Friday, March 14, 2014

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ትምህርት ታሪክ ሊሆን ነው


ከሰሜን ኮከብ
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የታሪክ ክፍል ( ዲፓርትመንት) መዳከሙን ስሰማ በጣም አዘንኩ። ዲፓርትመንቱ እኔ በነበርኩበት ጊዜም ፣ ከዘርና ከሃይማኖት ጋር በተያያዘ፣ ብዙ ችግሮችን ያስተናግድ ነበር። ኢህአዴግ ” ዲፓርትመንቱ የነፍጠኛው መመሸጊያ ዋሻ ሆኗል” በሚል ብሄር ብሄረሰቦች በብዛት እንዲገቡበት ይወተውት ነበር። አንድ የአማራ ተወላጅ ተማሪ ከፍተኛ ነጥብ ቢያመጣም፣ ከሌላው ብሄረሰብ ሰው ካልታጣ በስተቀር፣ መምህር ሆኖ የመቀጠር እድል አልነበረውም። በ1992 ዓም ነው፣ሁለት ሰቃይ ጓደኞቼ መምህር ለመሆን ያመለክታሉ። በጊዜው የዲፓርትመንቱ ሃላፊ የነበሩት ትግራዋይ ዶክተር ፣ሰቃዮቹን ትተው፣ አንድ የኦሮሞ እና አንድ የትግራይ ተወላጅ ምሩቃንን ይቀጥራሉ። አዲሶቹ ተቀጣሪዎች የነበራቸው ድምር ነጥብ ( Cumulative GPA) ጓደኞቼ ከነበራቸው ነጥብ በጣም ያነሰ ነው። በእንዲህ አይነቱ አሰራር ልባቸው የተሰበረው ጓደኞቼም እስከ ሴኔቱ ድረስ ክስ መሰረቱ፣ በመጨረሻ ያገኙት መልስ ግን ” የብሄር ተዋጽዎን ለመጠበቅ ሲባል የተወሰደ እርምጃ ነው” የሚል ነበር።
ለታሪክ ዲፓርትመንት መዳከም ዋናው ምክንያት የዘር ፖለቲካ የትምህርት ስርዓቱን መቆጣጠሩ ነው።
addis ababa un
በታሪክ ክፍለ ጊዜ ተማሪዎች ብሄርና ፖለቲካ ለይተው ሲደባደቡ አስታውሳለሁ ። የተወሰኑ የኦሮሞ ወይም የትግራይ ተወላጆች የተጻፉ ታሪኮችን ወይም ስያሜዎችን ለመቀበል እየተቸገሩ ከአስተማሪዎች ጋር ዘወትር ይጣሉ ነበር ። መምህራን “ማስተማር አልቻንልም” ብለው ስራ እስከማቆም የደረሱበት ጊዜም ነበር። ያም ሆኖ በማይነር ( በሁለተኛ ትምህርት) ከሚማሩት ውጭ፣ እጅግ በርካታ ተማሪዎች ታሪክ ያጠኑ ነበር ። ታሪክ ለመማር የመጡ ሌሎች አፍሪካውያንና ጥቁር አሜሪካውያንም ነበሩ። ተማሪው ከመብዛቱ የተነሳ ተወዳድሮ የማለፊያ ነጥብ ለማምጣት እጅግ ጭንቅ ነበር። አስተማሪዎችም የተማሪውን ፈተና አርመው በጊዜ ለመመለስ ይቸገሩ ነበር።
አንድ ገጠመኜን ላውጋችሁ። ነፍሳቸውን ይማርና ፕ/ር ሁሴን አህመድ የማጠቃለያ ፈተና ይፈትኑናል። የቀረቡልን ጥያቄዎች 4 ሲሆኑ መልስ መስጠት የሚጠበቅብን ለሁለቱ ብቻ ነው ። ለጥያቄዎቹ መልስ መጻፊያ ይሆን ዘንድ እያንዳንዳቸው 4 ገፆችን የያዙ ሁለት “ሉክ” ወረቀቶች ታደሉ። የጥያቄዎችን ማነስና የገፆችን መብዛት ስመለከት ” ምንድነው የምጽፈው” እያልኩ መጨነቅ ጀመርኩ። እኔ “የሸመደድኩትን” እያጠነጠንኩ ገና አንድ ገጽ ጽፌ ሳልጨረስ ከሁዋላየ የተቀመጠው ተማሪ 8ቱን ገጽ ጨርሶ ወረቀት እንዲጨመረው ጠየቀ፤ ሌሎችም እንዲሁ እያከታተሉ ወረቀት ጠየቁ፣ “በቃ ተሸውጃለሁ” ማለት ነው እያልኩ በድንጋጤ ወረቀቱን ለመሙላት ስል ብቻ እጽፋለሁ። መጀመሪያ ወረቀት ይጨመርንልን ያሉት ጓደኞቼ፣ የተጨመረላቸውንም ወረቀት ጨርሰው በድጋሜ ጠየቁ። አስተማሪውም “የመጨረሻ ወረቀታችሁ ነው” ብሎ አስጠንቅቆ ሰጣቸው። ” ፕሮፌሰር እኔ ጋ አራት የተረፉ ገጾች አሉና ከፈለጉ ልስጣቸው” ለማለት ሲዳዳኝ አንዱ ፈተናውን ጨርሶ ተነሳ፣ በዚህን ጊዜ ልቤ ከሁለት ተከፈለ፣ “ኤፍ” እንደምቅምም ገባኝ። ተስፋ የቆረጠ ሰው ማሰብ አይገደውምና መጻፌን አቁሜ ” እውነት ፕሮፌሰር የዚህን ሁሉ ታማሪ ወረቀት ያርመው ይሆን?’ እያልኩ ከራሴ ጋር ሙግት ጀመርኩ።
ትንሽ ቆይቶ ፕሮፈሰሩ ” you are left with 20 minutes only ” አሉ። በ 20 ደቂቃ ውስጥ፣ አንዳንዴም ቀረርቶ እየጨመርኩበት፣ 7 ገጾችን ጽፌ ለመምህሩ አስተያየት መስጫ ይሆን ዘንድ ግማሽ ገጽ አስተርፌ ተነሳሁ። ” ከሁለት ሳምንት በሁዋላ ፕ/ር ሁሴን ” ከ20 ገጽ በላይ የጻፋችሁ ተማሪዎች ወረቀታችሁን ወስዳችሁ እንደገና ጽፋችሁ አምጡ ብለው ሲያዙ ክፍሉ በሳቅ ተናጋ። እግዚሄር ይመስገን ውጤቱም እንደፈራሁት ሳይሆን ቀረ። ከ14 ዓመታት በሁዋላ ይህ የታሪክ ዲፓርትመንት ሰው አልባ ሆነ። ባለታሪኩዋ አገሬ ታሪክ አልባ ስትሆን ተሰማኝ።
ምንጭ፣  zehabesha.comhttp://www.zehabesha.com/amharic/archives/13602

No comments:

Post a Comment