Tuesday, March 11, 2014

አንድነት – የሚሊዮኖች ድምጽ ንቅናቄን በተመለከተ የአዉሮፓ ሕብረት አንድነትን አነጋገረ

በኢትዮጵያ የአዉሮፓ ሕብረት ልኡካን ቡድን መሪ አምባሳደር ቻንታል ሔበሬሽ፣ በአዉሮፓ ሕብረት የአፍሪካ ቀንድ እና የሕንድ ዉቂያኖስ አካባቢ ዴስክ ኦፌሴር ቪክቶሪያ ጋርሲያ ጉሌን እንዲሁም ቶማስ ሁይገባርቴስ የተሰኙ ፣ የአዉሮፓ ሕብረት ሃላፊ ፣ በነርሱ አነሳሽነት፣ ከአንድነት ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አባላት ጋር ሰፊ ዉይይት አደረጉ።
ከአንድ ሳምንት በፊት በኢትዮጵያ ስላለው የዲሞክራሲ ግንባታ ዙሪያ ከጠ/ሚኒስተር ኃይለማሪያም ደሳለኝ ጋር እንደተነጋገሩ የገለጹት የአዉሮፓ ሕብረት ባለስልጣናት፣ የአንድነት ፓርቲ በጠራዉ የሚሊዮኖች ድምጽ ሁለተኛ ዙር ንቅናቄ እንዳሳሰባቸው በመገለጽ፣ አንድነት በሚያደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ዙሪያ፣ ፓርቲው ፍቃደኛ ከሆነ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው፣ ጠይቀዋል።
የአንድነት ፓርቲ ወክለው ከአዉሮፓ ሕብረት ጋር የተነጋገሩት ሊቀመንበሩ ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራዉና የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊው አቶ ሃብታሙ አያሌው በበኩላቸው ያሉትን ሁኔታዎች ለማስረዳት ሞክረዋል።
አንድነት አሁን የሚያደርገው የሚሊዮነሞች ንቅናቄ ከዚህ በፊት ከተደረገው የቀጠለ እንደሆነ ያስረዱት የአንድነት አመራር ፣ ፓርቲዉ አዲስ አበባ ጨምሮ በ17 ከተሞች ፣ በፍትህ እና በላንድ ሪፎርም ዙሪያ ፣ ከሕዝብ ጋር ዉይይቶችን እንዲሁም ሰላማዊ ስለፎች እንደሚያደርግ ገልጸዋል። አንድነት ከዚህ በፊት ባደረጋቸዉ በርካታ ሰልፎች አንዳች አይነት በሰውም ሆነ በንብረት ላይ የደረሰ ጉዳት እንደሌለ የገለጹት የአንድነት አመራር አባላት ፣ ወደፊት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች፣ ሰላማዊና ሕዝባዊ እንደሚሆኑ በማስረዳት ፣ አንድነት አገር አቀፍ መዋቅሩን እያሰፋ እንደሆነም ለማሳየት ሞክረዋል።
የአዉሮፓ ሕብረት ተወካዮች፣ አንድነት ይዞት የተነሳዉ የመሬት ጥያቄ ተገቢና ወቃታዊ፣ ለኢትዮጵያ ጥቅም የሚያመጣ እንደሆነ የገለጹ ሲሆን፣ በመጪው የ2010 ምርጫ ዙሪያ አንድነት ያለውን አቋም እንዲያስረዳቸው ጠይቀዋል። «ለምርጫ አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረገን ነው። በሁሉም ክልሎች ለፌዴራልም ሆነ ለክልል ተወዳዳሪዎች ከወዲሁ እያዘጋጀን ነው» ሲሉ የመለሱት የአንድነት አመራሮች ፣ በምርጫ መሳተፉና አለመሳተፉ ግን ወደፊት የሚወሰን እንደሆነ ገልጸዋል። «ኢሕአዴግ ሁሉንም ነገር ከዘጋዉና የፖለቲካ ምህዳሩን ካጠበበው. የምርጫ ቦርድ የመሳሰሉ ተቋማት ገለልተኝነት ከሌላቸው፣ ምርጫ መሳተፉ ዋጋ እንደማይኖረዉ የገለጹት የአንድነት አመራራ፣ በምርጫዉ ጉዳይ፣ ኳሷ ኢሕአዴግ ሜዳ ላይ እንዳለች አስረድተዋል።
የፖለቲካ እስረኞችን ሁኔታ የጠየቁት የአዉሮፓ ሕብረት ተወካዮች «እስረኞችን ለመጠየቅ ይፈቅድላቹሃል ወይ ? » ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ፣ አንዱዋለም አራጌን አንድ ጊዜ ለመጠየቅ እንደቻሉ ነገር ግን ርዮት አለሙን፣ እስክንደር ነጋ እና ናትናኤል ሞኮንን እንዳይጠይቁ መከልከላቸውን የአንድነት አመራሮች አስረድተዋል።
በፊታችን ኤፕሪል በብራሰልስ፣ በአዉሮፓ ሕብረት እና በአፍሪካ ሕብረት መካከል ስብስባ እንደሚደረግ የገለጹት የአዉሮፓ ሕብረት ተወካዮች፣ የአንድነት ፓርቲ በስብሰባው እንዲገኝ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፣ በገዠዉ ፓርቲ ዘንድ የፊታችን ምርጫ ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ እንደሚሆን ቃል እንደተገባላቸው ተናግረዋል።
የአንድነት አመራሮች ግን ገዢዉ ፓርቲ የሚናገራቸውና ተግባራቶቹ አንድ እንዳልሆኑ፣ ይሄ ነው የሚባል፣ የዲሞክራሲ ግንባታዉን የሚያግዝ የተጨበጠ እርማጃ እንዳልወሰደ መረጃ ላይ በመደገፍ ገለጻ አድርገዉላቸዋል። «ጋዜጦቻችንን ማተም አልቻልም። ደጋፊዎቻችን ይታሰራሉ። ከሥራ ይባረራሉ። ሰልፍና ስብሰባዎች ስንጠራ ብዙ ጊዜ እንግልት ይደርስብናል» ሲሉም በአገዛዙ እየተፈጸሙ ያሉ ከፍተኛ የሰባአዊ መብት ጥሰቶችን ዘርዝረዋል።
በዉጭ አገር ስላሉ ኢትዮጵያዉያንም የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል። «በዉጭ ያለው ኢትዮጵያዊ ወደ 2 ሚሊዮን ይጠጋል። በርካታ ደጋፊዎች አሉን። በተለያዩ ቦታዎች በተለይም በአሜሪካ የድጋፍ ድርጅቶች አሉን» ያሉት የአመራሩ አባላቱ፣ የድጋፍ ድርጅት ዉስጥ የሌሉ፡ ነገር ግን የምናደርጋቸውን ከፓርቲ በላይ የሆነውን የሚሊየኖች ንቅናቄን የሚደገፉ በርካታ ኢትዮጵያዊ የሲቪክ እና የፖለቲካ ድርጅቶች እንዳሉም አስረድተዋል። የትግሉ አካል ከሆኑና በዉጭ ካሉ ኢትዮጵያዉያን ጋር ለመነጋገር፣ አንድነት የልኩካን ቡድኖች በቅርቡ ወደ ዉጭ እንደሚያስማራም ለአዉሮፓ ሕብረት ተወካዮች ገልጸዋል።
በአገሪቷ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት እንዲቻል የተሻለዉና የሰለጠነው አማራጭ፣ መነጋገር እንደሆነ ያስረዱት የአንድነት አመራር አባላት፣ አንድነት ከኢሕአዴግ ጋር ሆነ ሽብርተኞች ተብለው ካልተሰየሙ ደርጅቶች ጋር ሁሉ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ ለመነጋገር ፍቃደኛ እንደሆነ፣ ለዚያም ጥሪ እንዳቀረቡ ገልጸው፣ አገዛዙ ግን ቅድመ ሁኔታዎች እያስቀጠ በተደጋጋሚ ለመነጋገር ፍቃድኛ እንዳለሆነ ተናግረዋል።
ምንጭ፣ https://www.andinet.org/%e1%8a%a0%e1%8a%95%e1%8b%b5%e1%8a%90%e1%89%b5-%e1%8b%a8%e1%88%9a%e1%88%8a%e1%8b%ae%e1%8a%96%e1%89%bd-%e1%8b%b5%e1%88%9d%e1%8c%bd-%e1%8a%95%e1%89%85%e1%8a%93%e1%89%84%e1%8a%95-%e1%89%a0%e1%89%b0/

No comments:

Post a Comment