Sunday, March 26, 2017

የሰቆቃ (የቶርቸር) ጥቃት እና ወያኔ!


ሰሞኑን የቀድሞ የአንድነት የፖለቲካ ፓርቲ (የእምነተ አሥተዳደር ቡድን) አመራርና ቀደም ሲል በወያኔ እስር
ቤቶች በታሰረበት ወቅት በነበረበት ኢሰብአዊ አያያዝ ለከባድ ሕመም በመዳረጉ አሁን ላይ ለከፍተኛ ሕክምና አሜሪካ
የሚገኘው አቶ ሀብታሙ አያሌው በቅርቡ ለአሜሪካ ድምፅ የአማርኛው ዝግጅት ክፍል በሰጠው ቃለምልልስ ወያኔ
ሰብአዊና ፖለቲካዊ (እምነተ አሥተዳደራዊ) መብታቸውን በጠየቁ፣ የዜግነት ግዴታቸውን ለመወጣት ጥረት ባደረጉ
ንጹሐን ዜጎች ላይ እየፈጸመው ያለውን ሰቆቃ (ቶርቸር) መግለጹ ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጅ በመዘንጋት ይመስለኛል
ሀብታሙ በቃለ ምልልሱ ላይ ያልገለጻቸው ተጨማሪ አስከፊ የሆኑ የሰቆቃ ዓይነቶች በመኖራቸው ከሁለት ዓመት
ከመንፈቅ በፊት ቅሊንጦ እስር ቤት በነበርኩበት ጊዜ ከታሰርኩበት ክፍል ውስጥ ባገኘኋቸው ሁለት አንበሶች ማለትም
ስለሚወዳት ሀገሩና ሕዝቡ ሲል ለመግለጽ የሚከብድ ሰቆቃ ስለተፈጸመበት አበበ ካሴ እና በወያኔ አጠራር የጋምቤላ
ክልል ርእሰ መሥተዳድር ስለነበሩትና በወገናቸው በአኙዋኮች ላይ በወያኔ በተፈጸመው ጭፍጨፋ ምክንያት ወያኔን
ከድተው የፈጸመውን ጭፍጨፋ ለዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ ስላጋለጡት አቶ ኦኬሎ አኳዬ ጀብድ “የቅሊንጦ አንበሶች!”
በሚል ርእስ ጽፌው ከነበረውን ጽፉፍ አሰቃቂ ሰቆቃ የተፈጸመበትን የአበበን ክፍል ነጥየ ባስነብባቹህ ያለውን
ሁኔታ በሚገባ ለመረዳት ያስችላቹሀልና በሚል አቀረብኩላቹህ፡፡
ታች አምና ከእስር ቤቱ እንደወጣሁ ይሄንን ጽሑፍ ለንባብ ላበቃው የቻልኩት በራሴ ፍላጎት ብቻ ሳይሆን አበበ ካሴ
ማለትም ባለታሪኩ የተፈጸመበትን ኢሰብአዊ ግፍ ለሕዝብ እንዳደርስለት አደራ ብሎኝ ስለነበረም ነበር፡፡ ጽሑፉን
በማኅበራዊ የብዙኃን መገናኛ እንደለቀኩት የኢሳት ጋዜጠኛ ካሳሁን ይልማ ቃለ መጠይቅ አድርጎልኝ ነበር፡፡ ነገር
ግን በወቅቱ ግልጽ ባልሆነልኝ አሁን ግን ግልጽ በሆነልኝ ዕኩይና ጠባብ ምክንያቱ ቃለመጠይቁን በጽሑፉ ላይ
ታሪኩን ስለዳሰስኩት ሁለተኛው ሰው ማለትም በአቶ ኦኬሎ አኳዬ ላይ ብቻ እንዲያተኩር በማድረግ ዋነኛ የሰቆቃ
ሰለባ ስለሆነውና አስደናቂ ታሪኩ ሊነገርለት ይገባ ስለነበረው አበበ ካሴ እንዳነሣ ሳይፈቅድልኝ ቃለምልልሳችንን
ቋጨው፡፡