Saturday, March 8, 2014

ለአቶ ዓለማየሁ አቶምሳ ፍትሃትና ሽኝት ሲባል ቅዳሴ መቋረጡ ምዕመናኑን አሳዘነ


(ዘ-ሐበሻ) የኦህአዴድ ሊቀመንበርና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት የሆኑት ዓለማየሁ አቶምሳ የቀብር ስነ ሥነ ሥርዓት በቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን ዛሬ ተፈጸመ። የርሳቸውን ሞት ተከትሎም ዛሬ 5 ኪሎ በሚገኘው ቅድስተ ማርያም ቤተክርስቲያን የክልሉ ፕሬዚዳንትን ፍትሃትና በአዲስ አበባ ስታዲየም የተደረገውን የሽኝት መርሃ ግብር ምክንያት በማድረግ ከጠዋቱ 8:30- እስከ 9፡00 ሰዓት ማለቅ የነበረበት ቅዳሴ ተቋርጦ በጠዋቱ 7 ሰዓት ላይ መፈጸሙ ምዕመናኑን ማስቆጣቱን ለዘ-ሐበሻ የደረሱት መረጃዎች ያመለክታሉ።
Alemayehu Atomsa
ለአቶ ዓለማየሁ አቶምሳ ስንብት በአዲስ አበባ ስታዲየም ሲደረግ ቅርብ ቤተሰቦቻቸው፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች፣ የፌደራል መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ የተለያዩ ክልሎች የስራ ሃላፊዎች ከመኖሪያ ቤታቸው ጀምሮ እንዳጀቧቸው የገለጹት የዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደ የስንብት መርሃ ግብር ላይ ጠ/ሚ/ር ሃይለማርያም “አቶ ዓለማየሁ ደርግን ለመጣል የነበረውን ትግል በወጣትነታእው ጀምሮ ተቀላቅለው በተለይ ለኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲና ፍትህ ማግኘት የታገሉ፤ እስከ ሕልፈታቸው ድረስም ታግለው የተሰዉ ታላቅ ሰው ናቸው። እነ አቶ ዓለማሁ ቢሰውም ያፈሯቸው በሺዎች የሚቆጠሩ ተከታዮች ትግሉን ያስቀጥላልይ፤ በመሰዋታቸው ለቁጭትና ለላቀ ትግል የሚያነሳሳን ነው” ሲሉ አወድሰዋቸዋል።
የኢሕአዴግ መንግስት ሕገመንግስቱን በጣሰ ሁኔታ ፓርላማው ሳይሰበሰብ የሶስት ቀን ብሔራዊ ሐዘንና ባንዲራ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ በመላው ሃገሪቱ ማወጁ አነጋጋሪ በሆነበት ሰዓት በሃይማኖት ተቋማት ውስጥም መዋቅር በመዘርጋት ቅዳሴ እስከማቋረጥ መድረሱ ብዙዎችን አስቆጥቷል። “በዚህ ታላቅ ጾም ወቅት ልጆቻችንን ለማቁረብ በፓትሪያሪኩ መቀመጫ በቅድስተ ማርያም ቤተክርስቲያን ተገኝተን እያስቀደስን ባለንበት ወቅት ልጆቻችንን እንዳናቆርብ የአቶ ዓለማየሁ አቶምሳ ፍትሃትና ሽኝት አለብን በሚል ቅዳሴው 7 ሰዓት ላይ እንዲቋረጥ መደረጉ አስቆጥቶኛል” ሲል አንድ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ ምዕመን ለዘ-ሐበሻ ገልጿል።
alemayeu-atomsaበቅድስተ ማርያም ቤ/ክ የተገኙት ምእመናን “ባለስልጣኑ ሕይወታቸው በማለፉ እናዝናለን፤ እግዚአብሔር ገነትን ያውርሳቸው፤ ሆኖም ግን እኩለ ቀን ላይ ለሚደረግ ቀብር የእኛን መብት ጥሶ ቅዳሴውን ማቋረጥ አግባብ አይደለም” የሚል አቋም ያለቸው ምዕመናን “ይህ የሚያሳየው የመንግስትን በሃይማኖት ውስጥ ጣልቃ መግባትን ነው” ብለዋል።
“በባለስልጣኑ ፍትሃት እና ሽኝት ላይ ቤተክርስቲያን ሰው ወክላ መላክ ትችላለች፤ በዚህ ዓብይ ጾም ወቅት ልጆቻችንን ሳናቆርብ ቅዳሴ ማቋረጥ ግፍ ነው” ሲሉ ሌላው አስተያየት ሰጪ ለዘ-ሐበሻ ዘጋቢዎች ተናግረዋል።
አቶ አለማየሁ አቶምሳ በታይላንድ ባንኮክ በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ45 አመታቸው የካቲት 26 ቀን 2006 ዓመተ ምህረት ነው ያረፉት። በምስራቅ ወለጋ ቢሎ ቦሼ ወረዳ ከአባታቸው አቶ አቶምሳ ሚጃ እና ከእናታቸው ወይዘሮ አየለች ብሩ በ1961 ዓ.ም መወለዳቸውን ከዚህ ቀደም መዘገባችን አይዘነጋም።

No comments:

Post a Comment