Saturday, February 15, 2014

ኢሕአዴግ ግትርነቱን እንዳይቀጥል!… ከግርማ ካሳ

ከግርማ ካሳ
አቶ ዳንኤል ተፈራ በዋስ መለቀቃቸው፣ አቶ አሥራት ጣሴም መፈታታቸውን አነበብኩ። መጀመሪያዉኑ እነዚህ የአመራር አባላት መከሰስ ብሎም መታሰር አልነበረባቸውም። ሆኖም ግን ኢሕአዴግ ነገሮችን በማርገብ እንዲፈቱ ማድረጉ በአዎንታዊነት ተቀብዬዋለሁ። አዎ «የኢሕአዴግ አመራር አባላትን ጥሩ አድርጋቹሃል » እላለሁ። ይህ አይነቱን፣ መቀራረብን የሚያመጣ፣ ፖለቲካዉ የበለጠ እንዳይከር የሚያደርግ ተግብራትን እንዲፈጸሙ ነበር የሁላችንም ፍላጎት።
Daniel Teferaኢሕአዴግ በአገራችን እያደረጋቸው ያለው የልማት እንቅስቃሴዎች ሰፋፊና አስደሳች ናቸው። በአዲስ አበባ እየተሰራ ያለዉ የቀላል ባቡር ግንባታን ብቻ ከተመለከትን ከተማዋን ይቀይራል ተብሎ ይጠበቃል። ይህ የአዲስ አበባዉ የባቡር ፕሮጀክት 475 ሚሊዮን ዶላር ነው ወጭዉ። 85% ( 403 ሚሊዮን ዶላር) ከቻይና የኤክስፖርት-ኢምፕርት ባንክ ብድር የተገኘ ሲሆን፣ 15% (71 ሚሊዮን ዶላር) የሚሆነው ከመንግስት ካዝና የሚመጣነው የሚሆነዉ።
እዉነቱን እንነጋገር ከተባለ፣ በአንድ አመት በዉጭ አገር የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ፣ ኢትዮጵያ ከቻይና የተበደረችውን 403 ሚሊዮን ዶላር መዝጋት ይችላል። ቢያንስ 1 ሚሊዮን የሚቆጠር ኢትዮጵያዊ በዉጭ ይኖራል። በቀን አንዲት ዶላር ብቻ፣ ለአንድ አመት ከአንድ ወር እና 8 ቀናት ቢዋጣ 403 ሚሊዮን ዶላር ማግኘት ይቻላል።
ይህ በዉጭ የሚኖረዉ ሕዝብ በልማቱ እንቅስቅሴ ላይ ትልቅ ሚና ሊጫወት ያልቻለው፣ ኢሕአዴግን ስለሚቃወም ነዉ። ኢሕአዴግን የሚቃወመው ደግሞ በሌላ በምንም አይደለም፣ በአገር ቤት በሚታዩ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ በሚታዩ የሰብአዊ መብት ረገጣዎች በመሳሰሉት ነዉ።
Andu5
ኢሕአዴግ ተቃዋሚዎችን እንደ ጠላት ከማየት (በተለይም አንድነት ፓርቲን) ተቃዋሚዎች ጋር አብሮ መስራት ቢችል፣ በጋራ አገራዊ በሆኑ ፕሮጀክቶች ላይ ግልጽነትና ተጠያቂነት ባለበት መልኩ የነአንድነት ድጋፍ ቢያሰባስብ፣ በቀላሉ የዳያስፖርዉን ፖለቲካ መቀየር ይችል ነበር። አስቲ አስቡት፣ በነአንድነትና በኢሕአዴግ መካከል መግባባቶች ተፈጥረው፣ ያሉ ልዩነቶች ሁሉም አሸናፊ በሆነበት መልኩ ተፈተዉ፣ የጋራ ኮሚቴ አቋቁመው፣ በጋር ተወካዮች ወደ ዉጭ ልከው፣ በአገራችን የሚደረገዉን ልማት ለማፋጠን ሕዝቡን ቢያነጋገሩ፣ አዳራሾች አይሞሉምን ? ጢቅ ነበር የሚሉት። እንደዉም በቀዳሚነት ስብሰባዎችን የምሳተፈውና የማስተባበረው እኔዉ እሆን ነበር።
እንግዲህ ለዚህ ነው የነ አስራት ጣሴ መፈታትን እንደ ጥሩ ጅማሬ የወስድኩት። በቶሎ ኢሕአዴግ እነ አንዱዋለም አራጌ፣ እስክንደር ነጋ፣ ርዮት አለሙ የመሳሰሉትን መፍታት አለበት። ፈረንጆች እንደሚሉት ፣ It is long overdue:: በቶሎ ከነአንድነት ጋር ለመነጋገር መዘጋጀት አለበት።
ኢሕአዴግ በወረቀት ያስቀመጣቸው እቅዶች፣ ትላልቅ እቅዶች ናቸው። ይመስለኛል ፣ አንዳንድ ቦታ ማስተካካያዎች ለማድረግ ይፈልጉ ይሆን እንጅ፣ በመርህ ደረጃ አንድነቶችም የሚቀበሏቸው ናቸው ብዬ አስባለሁ። የአመራር አባላቱ የአባይን ግድብ ከልብ እንደሚደግፉ ሲናገሩ ሰምቻለሁ። ቦንድም የገዙም አሉ።
እንግዲህ ኢሕአዴግ የፖለቲካ ምህዳሩን ያስፋ፣ እስረኞችን ይፈታ እያልኩ፣ እነ አንድነትም በልማቱ እንቅስቅሴ ዙሪያ ከዚህ በፊት እንደሚያደርጉት ከኢሕአዴግ ጎን ይቁሙ እላለሁ። አገርን በሚጠቅም መንገድ ከኢሕአዴገ ጋር መስራት ተገቢ ነዉ። አዲስ የተመረጠዉ የአንድነት አመራርም በዚህ ጉዳይ የአብሮ የመስራት ጥቅምም በይፋ ያስቀመጠው ነዉ።
Ryot Alemu
እዚህ ላይ ከኢሕአደግ ጎን ይቁሙ ስል፣ ጭፍን ድጋፍ ይሰጡ ማለት አይደለም። በሙስና በመልካም አስተዳደር እጦት የሚኖሩ ምዝበራዎችን፣ በግንባታዉ ወቅት ያሉ የጥራት ጉድለቶችን መከታታልና እንዲታረሙ ግፊት ማድረግ ይኖርባቸዋል። ይህን አይነቱ ብልሹ አሰራርን ማጋለጥ ይጠበቅባቸዋል። እነርሱም ደግሞ ስልጣን ከያዙ፣ አሁን ያሉትን የኢሕአዴግ እቅዶች እንዴት በተቻለ ሁኔታ እንደሚቀጥሏቸው፣ እንዴት እንደሚያሻሽሏቸው፣ ሌላ አዲስ እቅድ ካላቸው ምን ምን እንደሆኑ አማራጮች ማቅረብ አለባቸው። ( በዚህ ጉዳይ ላይ አዲሱ የአንድነት አመራር ከመቃወም ፖለቲካ ያለፈ ግልጽ አማራጭ ፖሊሲዎችን እያዘጋጀ እንደሆነ ነዉ የሚጠቁሙ አንዳንድ ፍንጮች አሉ)
አንድነቶች ከኢሕደግ ጎን ይቁሙ ስል፣ ከዚህ በፊት ኤዴፓ ሲያደርግ እንደነበረው፣ የኢሕአዴግ ጎጂ ፖሊሲዎቹን አይቃወሙ ማለት አይደለም። ኢሕአዴግ በልማቱ ዙሪያ ጥሩ ነገር ቢያደርግም፣ የሚያራምዳቸው የጎሳ ፖለቲካ፣ በ ኤርትርና በወደብ ዙሪያ ያለው አቋም፣ በመሬት ፖሊሲ፣ በዉስጡ በሚታዩ የስልጣን መባለጎች እና ሙስናዎች በመሳሰሉት ጉዳዮች ዙሪያ በጠነከረና በተደራጀ መልኩ መቃወም የግድ ነው። ሕዝብን ከጀርባዉ በማሰለፍ፣ ሕዝባዊ ሰብሰባዎችን፣ ሰላማዊ ሰልፎችን፣ የሥራ ማቆም አድማዎችን የመሳሰሉ ሰላማዊና ሕጋዊ እንቅስቅሴዎችን በማድረግ የኢሕአዴግ ጎጂ ፖሊሶዎች እንዲስተካከሉ ግፊትና ጫና ማድረግ አለበት። ይህ ነው እንግዲህ የሰለጠነ ከጥላቻ የጸደ ፖለቲክ የሚባለው። መልካም ሥራን እየደግፉ፣ ክፋትን አጥብቆ መቃወም።
በመጨረሻ ኢሕአዴግን በልማቱ እንቅስቃሴ እንደግፍ ማለቴ ሊያስቆጣቸው የሚችሉ ሊኖሩ እንደሚችሉ ይገባኛል። አልፈርድባቸዉም። ነገር ግን በሂደት የመቀራረቡና የመነጋገሩን ጥቅም ሲያዩ፣ እስረኞች ተፈተው በአንጻራዊነት ዴሞክራቲክ የሆነ እንቅስቃሴ እየተደረገ እንደሆነ ሲያነቡ፣ ለዘብ ይላሉ ብዬ አስባለሁ።
እንደጠበቅነው ኢሕአዴግ አንድ እርምጃ ወደፊት መጥቶ፣ ሁለት እርምጃ ወደ ኋላ ከተመለሰ፣ ግትርነቱን ከቀጠለ፣ አንድነትም ሆነ ሌሎች ከሕዝቡ ጋር በመሆን ትግላቸዉን ይቀጥላሉ። ምን ጊዜም ደግሞ አሸናፊ የሚሆነው ህዝብ ነዉ።
ምንጭ፣ http://www.zehabesha.com/amharic/archives/12815

No comments:

Post a Comment