Saturday, December 14, 2013

ኃያሉ አፄ ሚኒሊክ ለሴቶች እኩልነት ተግባራዊነት ዓለምን የቀደሙ ንጉሥ


ከሥርጉተ ሥላሴ 
ስርጉተሥላሴ
ስርጉተሥላሴ
ያን ዘመን ሳስበው ዛሬን መስለችን ያስለቅሰኛል። ያን ፈርጣማ ዘመን ሳስታውሰው ዛሬ ውስጣችነን መሳሳቱ ያቃጥለኛል። ያን ገድላማ ብቁ፣ ሥልጡን፣ ልዑቅ የአመራር ጥብብ ሳናግረው ግን መጽናናትን፣ ሙላትን ያጎናጽፍልኛል። ክብራቻን፤ ማንነታችን፤ ተፈሪነታችን፤ መሪነታችን፤ ብልህነታችን፤ እርግጠኛ ያደረጋል፤ የቀደምቶቹ ብቃት የሰማይ ገደል ለዛሬ ፍንጣቂ ማስተዋል ቢልክልን አምላኬ ምን አለበትም እላለሁ። የባዕዳን ግራሞት ጭብጥ፤ የእርስ በርስ ችግራችውን ዋጥ አድርገው በጋራ ቆመው ትንግርትን ሰማዕታት ማዘከራቸው የህሊናችን ዳኛ ሆኖ እኛን ሊገራን ባለመቻሉ ግን የልቤ ክናድ ይላል። ነገ ሌላ ቀን ነውና ነገን እንዲመርቅልን ህይወቱ ያላቸው አበው ሱባዬ ቢይዙበት ምኞቴና ናፍቆቴ ነው … አንደ ዕምነታቸው።
ዓለም ስለ ሴቶች ብቃት ብጣቂ እውቀት ባልነበረበት ጊዜ የኛው አፄ ኃያሉ ንጉሥ ሚኒሊክ ደማቸው – መንፈሳቸው – ሙሉዕ ፈቃድ ሰጥቶ ተግባር ላይ የዋለ በኽረ ጉዳይ ነበር የሴቶች እኩልነት። ኢትዮጵያ ሚስጢር ናት። ኢትዮጵያ ገድል ናት። ኢትዮጵያ ዓለም – ዓቀፍ ህግ ናት።  ኢትዮጵያ የቀደመች ሥልጡን መምህርት ናት። በዘመኑ የጣሊያን ተጋነት፤  የኢትዮጵያ ጥበበኛው መሪ የአፄ ሚኒሊክ አመራር ደግሞ ዕርቅና ሰላም ፈላጊነት ዓለምን ያሰደመመ መረቅ ትውፊት ነበር። ምርኮኛን ተንከባክቦና መርቶ ወደ ሀገሩ መሸኘትም አብነታዊ የአፄ ሚኒልክ ልዑቅ በኽረ ተግባር ነበር። ዛሬ ያሉት ሰበነካዊ ዓለምዓቀፍ ድርጅቶች መሰረተ ጥንስስ ብቻ ሳይሆን ዓላማው ቀድሞ ኢትዮጵያ መሬት ላይ በድርጊታ ላይ የዋለው በድንቅነሽ አንባ ነበር – በብጡሎቹ።
ሀ. የእኩል ተሳትፎ ፈቃድ … ለሴቶች።
የጣሊያን ከመቀሌ አልፎ መስፋፋትን መመረጡ ያልተማቻቸው ንጉሥ ሚኒሊክ አልጋቸውን ለአጎታቸው ለራስ ዳርጌ አደራ ሰጥተው፤ ረዳትም ደጃዝማች ኃይለማርያምንና የወህኒ አዛዡን ወልደ ጻድቅን ጨምረው ሊነሱ ሲያስቡ ባለቤታቸው እቴጌ ጣይቱ አልለይም ሲሉ ሙሉ እምነትና ፈቃድ ሰጡና እቴጌ ጣይቱ አብረው ዘመቱ። „ … ከጃንሆይ ጋር እቴጌ ጣይቱ አልለይም ብለው ጦራቸውን ይዘው ተጓዙ“ (ገጽ 100*)  „ „ወንድ ያለ ዕለት – በዕለት፤ ሴት ባለ በዓመት“ የሚለውን የሴቶችን መብት ደፍጣጭና ተጫኝ ኮስሳ ብሂል ቅስሙን እንኩት አድርገው የአካላቸውን ክፋይ የማይገሰስ ክብር ሰጥተው፤ ፈቃዳቸውንም ተንከባባክበውና አልምተው የታሪክ ዐይነታ ታዳሚ አደረጉት። ዘመናቸውንም ሙሉና ጌጣማ አደረጉት። የቀደመና የሰለጠነ መክሊት ባላጸጋው የንጉሦች ንጉሥ አፄ ሚኒሊክ የተግባር ምሰሶና ዋልታ ነበሩ ለሁለመናችን።
minilikለ. የጦር ጄኒራልነት፣ የአዋጊነት፣ የመሪነት፣ የአዝማችነት ጥንድ የእኩልነት ዕውቅና እና ዕሴቱ – ለሴቶች።
 ዓለምዓቀፉ የቅኝ ግዛትን ቅስም የሰበሩት ክቡር አፄ ሚኒሊክ „ሴትና አህያ በዱላ“ የሚለውንም ሥነ – ቃል ጨፍልቀው ከጠላት ጋር ለጦርነት ዐዲማህለያ ላይ በ10 ግንባር ካሰለፉት 30 ሺህ ጦር ውስጥ የልዕልታችን፤ የንግሥታችን  የእመቤት ጣይቱ ግንባር ከ3ሺህ ጦር ጋር አንዱ ግንባር ነበር። ይህ በዬትኛው የዓለም ታሪክና መዘክር የሚገኝ ጣዝማዊ ገቢር ነው። ማንም ሀገር እንዲህ በዚያ ዘመን የተግባር ዲታ የሆነ የሴቶች የእኩልነት ታሪክ የለውም። አባታችን፤ መሪያችን፤ መኩሪያችንና ንጉሣችን አፄ ሚኒሊክ ግን እኩልነትን የተቀበለ፤ እኩልነት በድርጊት ያዋለ፤ እኩልነትን ያከበረ – ያስከበረ – ያደመጠ፤ እኩልነትን በጥንግ ድርብ ካባ ያንቆጠቆጠ የመኖራችን ልዩ የታሪክ ጉልላት እንዲያብብ ፈቀዱ።
ስለዚህ አፄ ሚኒሊክ ለእኛ ለኢትዮጵያ ሴቶች ብቻም ሳይሆን ዓለምን በድርጊት ያስተማሩ ድንቅ የኢትዮጵያዊነት አንዱ ታላቅ ሚስጢር ናቸው። ንጉሥ ሚኒሊክ ለሴቶች እንደ አደራጅነተቻው የክብር አባላችን ሰንደቃችን ናቸው።
ኃያሉ የአፍሪካ ቀንዲል ንጉሥ ሚኒሊክ የሴቶችን የብቃት ሚስጢር መንፈስ ቅዱስ ስላቀበላቸው ውጤቱ አዲስ የጥቁር  የማይደፈር የድል ፕላኔት ሆነ። በውጊያውም ሳይደክሙ እቴጌ ጣይቱ ከአካላቸው ጎን ሆኑ በፋመው ውጊያ ላይ “ …  በዚህ ጊዜ ዐፄ ሚኒሊክ የጦር ወታደራቸውን በሚያበራታታ ቃል ሲያደፋፍሩ፤ እንዲሁም እቴጌ ጣይቱ እንደ ወንድ በጦርነቱ መካካል እዬተላላፉ የቆሰለውን ሲያነሱ፤ ለተጠማው መጠጥ፤ ለተራበው ምግብ ሲሰጡ ዋሉ“* ይሉናል ሊቁ ጸሐፊ (ገጽ 110 )የተደራጀ የቀይ መስቀል ተግባር በእናትነት ተፈጥሯዊ ክህሎት በቅሎ፤ በአጋርነት ጸድቆ፤ እንሆ … ሚስጢር ይቀዳል ከድንቅነሽ አንባ …. ከእግዚአብሄር በታች እኩልነታችን ያፀደቁ ብቸኛ መሪ፤ የእኩልነታችን መሸሸጊያ የልብ አድርስ እረኛ ፤ አስተዋሽ ጌታ ንጉሥ ሙሴ አፄ ሚኒሊክ።
ሐ. የእቴጌ ጣይቱ ብርሃነ ዘ ኢትዮጵያ በፖለቲካ እኩል የመወሰን አቀም ይለፍ በሀሴት ያረገበት ዕውነት፤
  “ሴት ቢያውቅ በወንድ ያልቅ“ ተረት ሆኖ ቀራንዮ የዋለበት ሌላው ትርጉም እቴጌ በባለቤታቸው የነበራቸው የላቀ ተደማጭነትና ተቀባይነት ነበር። ሴትነት ሰማይ ያረገበት ልበለው ከቶ? የአማካሪነት ልዩ ፈቃድ በገፍ ማግኘትና የመደመጥ እርግጠኝነት በልበ ሙሉነት መለገስ … አፄ ሚኒሊክ ለእቴጌ ጣይቱ ወደው ሰጡ። በጠባያቸው፣ በብልህነታቸው፣ በጣም ይወዷቸውና ያከብሯቸው ስለነበረ አብዛኛውን ጊዜ ውሳኔው የሚፀናው በእቴጌ ጣይቴ እንደ ነበረ ሊቁ ተክለጻድቅ መኩሪያ እንዲህ ይገልጡታል“ … አቴጌ የጠሉት ይነቀፋል ከሹመትም ይሻራል፤ የወደዱትም በንጉሰ ነገሠቱ ዘንድ ክብርና ሹመትም ያገኛል። ስለዚህ መሳፍንቱንና መኳንነቱ ንጉሡ ነገሥቱን እንደሚፈሩና ደጅ እንደሚጠኑ ሁሉ እንዲሁም እቴጌዪቱንም ደጅ ይጠኑ ነበር።  ዋው! ቅቤ የሚያጠጣ አንጀት የሚያረሰርስ ተመክሮ ነው። እንዴት ድንቅ ፈለፈል የሆነ ውብ ጥልፋማ ዘመን ነበር።
„ሴትና አይህያ … „ ቀርቶ … ውሳኔ የማመንጨት፤ የማሻሻል፤ የመሰረዝ የብቃት ልኬታን ይለፍ የሰጠው፤ እንዲሁም  የእቴጌ በራስ የመተማማን ስኬታማ ጉዞ  … ሲፈተሽ ደግሞ  „ይልቁንም የውጫሌ ውል የ17ኛው አንቀጽ ንግግር እንዲለወጥ በዐፄ ሚኒሊክና በኮንቱ አንቶኔሊ መካካል ክርክር ሲደረግ እቴጌይቱ በክርክሩ እዬገቡ ይነጋገሩበት ነበር። በኋለም በ 17ኘው አንቀጽ ንግግር ፈንታ የኢትዮጵያ ንጉሠ – ነገሥት ከመሬቱ አንድ ክፍል ወይንም በ17ኛው አንቀጽ የተባለውን ጥገኝነት ለሌላ ለውጭ አገር መንግሥት እንዳይሰጥ  ግዴታ ይግባና ይለወጥ ብሎ ሲያቀርብ …  ንጉሠ ነገሥቱ ይህንን ሃሳብ ከራስ መኮነን ጋር ሲመካካሩ እቴጌይቱ የፈቀድነውን ብናደርግ የኛ የግል ሥልጣናችን ነው እንጂ እሱን በፍጹም የሚያገባው ነገር የለም ብለው ውሉ እንዲቀር አደረጉ“ (ገጽ 131 እና 132)*
Emperor Menelik II sይህን ያህል ክብራችን ንጉሥ ሚኒሊክ ፍጹም የሆነ ሙሉ እምነት በሴቶች ብቃትና የመወሰን አቅም ነበራቸው። የሴቶችን ማንም ሊጋረው የማይችለውን የእናትነት ሰማያዊ ጸጋ ሥራ ላይ የዋሉ ብቸኛ ንጉሥ። ስለሆነም ሀገራቸውን፤ ሰንደቃቸውን ዳር ደንባራቸውን አስከበረው ተከበሩ። ምክር ስለ አዳመጡ ፍላጎታቸውን እውን አድርገው በሥልጣኔ ጎዳና እናት ኢትዮጵያን መሩ። ነፃነታችን በድል ስላቀለሙት አንገታችን ደፍተን ከመኖር ታደጉን። ተፈሪ፤ በራስ ቋንቋ የምትናገር፤ በቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ አፍሪካዊት ሀገር፤ በራሷ ፊደል የምትጽፍ ሀገር፤ የጥቁር መመኪያና መጠጊያ፤ የእኔ የምትለው ህግ – ባህል – ወግ – እምነትና ልማድ ያላት ውብ ሀገር በደማቸው ሸለሙን። ቅይጥና የትውስት ነገር አልነበረንም። ሁለመናችን ጠረኑ እኛን ይመስል ነበር። የዛሬን አያድርገው አረሙ ወያኔ ለባዕድ እስከ ሸጠው እስከለወጠው ዱድማ ዘመን ድረስ ….። ክብራችን እናመሰግነዎታለን። ጌታችን እንወደወታለን ጸሐያችን፤  እመቤታችን ብርሃነ ዘ ኢትዮጵያ …. እቴጌ ጣይቱም የድርጊት ጀግንነተወት የተስፋችን ማህደር ነውና እናፈቅረወታለን። አላሰፈሩንም። ይልቁንም ድፈርትን አዋጡን እንጂ ….
ይቋጭ መሰል … ደግመን ያለገኘው እድል ነው ኃያሉ ሚኒሊክ በዛ ዘመን ሰጥተውን የነበረው። የእኩልነት ዕውቅና፤ የመኖር ነፃነት ኪናዊ ቃና። አፄ ሚኒሊክ ለሴቶች ተቀድቶ የማያልቅ ባለውለታ፣ ክንድና ደጅን ነበሩ።ይህ ዝቀሽ ታሪክ የሀገርን ዳር ደንበር በማስከበር ብቻ የተወሰነ አልነበረም። ለሰው ልጆች መብት ማስከበሪያ የዲሞክራሲ ሂደት ልዕል ጉልትም ነው ትምሀርት ቤት።
በዘመኑ በነበሩ ሌሎች መንግሥታዊ አስተዳደሮችና መዋቅሮች አመሰራረት ሆነ አመራር፤ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሥልጣኔ ጉዞ እርምጃ በተሰጣቸው የእኩልነት መብት እቴጌ ጣይቱ መጠነ ሰፊ ተግባራትን በመከወን የሴቶች ኮከብ፤ እመ ብዙኃን መሆን ችለዋል። ስለሆነም እቴጌ የናሙና የተግባር ተቋም ነበሩ። ያገኙትም ዕድል ባክኖ አልቀረም።  በአግባቡ በብልህነት ተጠቅመው ጸጋቸውን ዓለም እራሱ እንዲመሰክርበት አድርገዋል። የሰከነው ተሳትፏቸው በተግባር ከብሮ ሀገርን ያህል ዕንቁ ነገር አተረፈ። ትውልድን ገነባ። በነገራችን ላይ የቀደመው የእናት ሀገራችን ምስላዊ ካርታ እኮ እንደ ሌሎች ሀገሮች ቅኝ ለማደረግ ባሰበት ተሰመሮ የተሰጠን አልነበረም። በፍጹም! በደምና በአጥንት የጸደቀ አልማዝ እንጂ …. ። ይህ አዲሱ ዜማ „ጣይቱ የኛቱ“ ትንቢት ዕውን ከሆነ ኢትዮጵያዊነት እንደ ገና ያበራል። ተስፋ አያልቅ … ም። በመጨረሻ — አብሮነት ደስ ይላል – ያሳምራል … በመንፈስ ሃዲድ ለነበረን ቆይታ ትህትና ከአክበሮታዊ ምስጋና ጋር ሸለምኳችሁ።
ማሳሰቢያ  በትምህርተ ጥቅስ ባሉት ሥንኞች ውስጥ በጉልህ የተጻፉትና የተሰመረባቸው ኃይለ ቃላት፤ የበለጠ ለማሰረገጥ ብዬ እኔ እንጂ መጸሐፉ ላይ የለውም። በትምህርተ ጥቅስ ውስጥ የሚገኙት ኮከብ ያለባቸው አገላለፆች ሁሉ ገፃቸው ከላይ ተጽፏል፤ የደራሲው ሥምና የመጸሐፉ እርእስ ሲደጋጋም እንዳትሰለቹ በማለት ከላይ አልጻፍኩትም።
( በ1936 ዓ.ም የኢትዮጵያ ታሪክ – ከዐፄ ቴወድሮስ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከሊቀ ሊቃውነቱ ክቡር ተክለ ጻድቅ መኩሪያ መጸሐፍ የተወሰደ ነው) ከትህትና ጋር ..
ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ለዘለዓለም ያዘራሉ!
እግዚአብሄር ይስጥልኝ::
ምንጭ፣ http://www.zehabesha.com/amharic/archives/10860

No comments:

Post a Comment